ከንቲባ አዳነች አቤቤ ለከተማው ምክር ቤት ባቀረቡት ሪፖርት፤ የከተማ አስተዳደሩ ለትምህርት ዘርፉ በሰጠው ልዩ ትኩረት የተማሪዎችን ተደራሽነት፣ አካታችነትና የትምህርት ጥራት በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ መቻሉን አስረድተዋል። በዘርፉ የተመዘገቡ ዋና ዋና ስኬቶች ፡-
•የተደራሽነት ዕድገት፡- ባለፉት አምስት ዓመታት የተማሪዎች ቁጥር ከ829,158 ወደ 1,334,830 ከፍ ብሏል። በ2018 በጀት ዓመትም ይህንኑ የተማሪዎች ቁጥር በማሳካት ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ81,093 ብልጫ ማሳየት ተችሏል።
•የትምህርት ጥራትና ውጤት፡- ጥራትን ለማረጋገጥ በተሰራው ስራ የ6ኛ ክፍል ከተማ አቀፍ ፈተና አላፊዎች ከ80.2% ወደ 97%፣ የ8ኛ ክፍል ከ36.1% ወደ 96.2%፣ እንዲሁም የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና አላፊዎች ከ25.45% ወደ 31% ማደጉን አብራርተዋል።
•የትምህርት ግብዓት አቅርቦት፡- የመፅሐፍና ተማሪ ጥምርታን 1፡1 ማድረስ የተቻለ ሲሆን፤ የደብተርና ዩኒፎርም አቅርቦትም ትምህርት ከመጀመሩ አስቀድሞ በክረምቱ ሙሉ በሙሉ ለተማሪዎች ተደራሽ ሆኗል።
•አካታች ትምህርት፡- የልዩ ፍላጎት ትምህርትን በማስፋፋት 124 ማዕከላት ተደራጅተው 34,117 ተማሪዎች የትምህርት ዕድል አግኝተዋል። ለአይነ ስውራንና ለልዩ ፍላጎት ተማሪዎች የብሬል መፃህፍት፣ የድምጽ መሳሪያዎች እና የተለያዩ የአካል ድጋፍ ግብዓቶች ቀርበውላቸዋል።
•የትምህርት ለትውልድ ንቅናቄ፡- ማህበረሰቡን በማስተባበር 13 ቢሊዮን ብር የሚገመት ሀብት (በገንዘብ፣ በአይነት፣ በጉልበትና በእውቀት) በማሰባሰብ የትምህርት ቤቶችን የመጠገንና ግብዓት የማሟላት ስራ መሰራቱን ከንቲባዋ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት ማብራሪያ ሰጥተዋል።
.