የብሬል መጽሐፍ ግምገማው በከተማ አስተዳደሩ ከሚገኙ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ብቃታቸው ተረጋግጦ በተመረጡ አይነስውር መምህራን እና ከቢሮው ጉዳዩ በሚመለከታቸው የስርአተ ትምህርት ባለሙያዎች እየተካሄደ መሆኑን ከስራ ክፍሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ የልዩፍላጎትና የጎልማሶች መሰረታዊ ትምህርት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ገመቺስ ፍቃዱ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ልዩ ፍላጎት ላላቸው ተማሪዎች ፍትሐዊ ትምህርት ተደራሽ ለማድረግ የተለያዩ ተጨባጭ እንቅስቃሴዎችን በማድረግ ላይ መሆኑን ጠቁመው በዛሬው እለት መካሄድ የጀመረው የ1ኛ ደረጃ የብሬል መጽሐፍ ግምገማ አይነስውራን ተማሪዎች በትምህርታቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ከተማ አስተዳደሩ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ማሳያ መሆኑን አመላክተዋል።
ዳይሬክተሩ አያይዘውም የብሬል መጽሐፍ ግምገማው ሲጠናቀቅ የሚሰጡ የማስተካከያ ሀሳቦችን በማካተት ታትመው ለተማሪዎች ተደራሽ የሚደረጉ መሆኑን ገልጸው ቀደም ሲል ለ2ኛ ደረጃ ተማሪዎች የተዘጋጁ የብሬል መጽሐፍት እና የመምህሩ መምሪያ በተመሳሳይ መገምገሙን አስረድተዋል።
.